Wednesday, May 29, 2013

እግዚአብሔር አይችልም

እግዚአብሔር አይችልም
በታላቅ ግርማ በማይመረመር እውቀትና በማይቆጠር ጥበብ ለአኗኗሩ መነሻ ለዘመኑ ፍጻሜ የሌለው ብቸኛው አምላክ እግዚአብሔር ነው:: ምንም እንኳ ምድራችን ራሳቸውን በሠራዊት ብዛት፣ በዘመነኛ የጦር መሣሪያና ስልት ያስታተቁ ታላላቅ ተብዬዎች የበዙባት ብትሆንም ትልቅነታቸው ከጌታችን ጋር አይነጻጸርም:: “ጌታችን ታላቅ ነው ኃይሉም ታላቅ ነውና”  እንዲሁም ዓለም የሠለጠነ የሰው ኃይል ቢያከማች የረቀቀ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ቢጠቀም ኃይሉ ግን የሚመጠን፣ የሚለካና የሚገደብ እንዳይቋረጥም ከፍተኛ ጥንቃቄ በተመላበት ቁጥጥር የሚጠበቅ ነው፡፡ የጌታችን ኃይል ግን ከዚህ ይለያል:: ታላቅ ነውና፡፡”እግዚአብሔር ታላቅ ነው” አምላካችን ታላቅ  የተባለው እንደ ፍጥረት ሥርዓት  የሚለካበት መለኪያ ኖሮት አይደለም፡፡በጠንከራ ክንዱ ጊዜና ሥልጣን፣ሐብት፣ትዕቢትና ዕውቀት ያተለቃቸውን ሁሉ በረቂቅ ጥበቡ የሚያሳንስ  እርሱ ስለሆነ ነው፡፡  የቋንቋችንም አድማስ ከዚህ ቃል ማለፍ አይችልም፡፡ ደግሞስ “አቤቱ አንተ ብቻህን ታላቅ አምላክ ነህ” አይደል የተባለው፡፡መዝ 95፥4፣85፥10
አዎ የእኛ ጌታ እጁን ዘርግቶ ይቅርና ከአንደበቱ ቃል ሳይወጣ በልቡ ፈቃድ ብቻ የገዘፈውን ሰማይና ምድር የሠራ ነው:: በየትኛውም ዘመን ትውልድ የአስተሳሰብ እድገት ሊደርስበት የማይችል ብርሃንን በይሁንታ የፈጠረ ነው፡፡ ለምድር ኪስ አበጅቶ ሰፊ ባደረገው ኪሷ ያስቀመጠውን ውሃ ውቅያኖስ ያለው በጠባቦቹ ኪሶቿ ያስቀመጠውን ውሃ ደግሞ ባሕር  እያለ የጠራው  እርሱ ነው :: ዘርዝረን የማንፈጽመውን ሥራዎቹን ያከናወነበትን ኃይል ደግሞ ከነቢዩ ጋር “ኃይልህ ታላቅ ነው አንተ ባሕርን በኃይልህ አጸናሃት” እንዲሁም “ኃይልህ ብዙ ነው” እንለዋለን፡፡ መዝ 65፥3 ፣73፥13
እግዚአብሔር እርሱ ሠርቶ ይቅርና ሲያሠራም ኃይሉ ታላቅ ነው:: በሙሴ በትር ላይ የተገለጠው ኃይሉ ባሕር ሲከፍል ከዓለት ላይ ውሃ ሲያፈልቅ በእምነት አይተናል:: በእስራኤል ጩኸት ውስጥ የኢያሪኮን ቅጥር /ግንብ/ ሲያፈርስ አስተውለናል:: “ለእግዚአብሔር ዘምሩ የኃይል ቃል የሆነ ቃሉን እነኾ ይሰጣል” ተብሏል  መዝ 67፥33:: ደግሞስ “እንደ እግዚአብሔር ያለ ማንም የለም” የተባለው በእውነት እንደርሱ ያለ ማንም ስለሌለ ነው :: የባሕሩን ኃይል ሲገዛ ሞገዱንም ጸጥ ሲያደርገው ነፋሱንም ሲገስጽ በፈጠረው ፍጥረት ላይ ከፍተኛው ባለሥልጣን እርሱ ብቻ መሆኑን አስታውቋል:: ፍጥረት ሁሉ የኃይሉ መገለጫ የጥበቡ ማስታወቂያ ነው:: መዝ 88፥9፣ ማቴ 8፥23፤ 27::
እግዚአብሔር ለሚያምኑትና ለሚታመኑበት  ሁሉ ነገሮችን የሚያከናውንበት ኃይል ከጠላት የሚከለሉበት ጋሻ መሆኑን “እግዚአብሐር ኃይሌና ጋሻዬ ነው ልቤ በእርሱ ታመነ እኔም ተረዳሁ” በሚለው ዝማሬ መገንዘብ ጠቃሚ ነው መዝ 27፥7:: የሰው ልጅ በራሱ አንዳች ኃይል ስለሌለው ከአምላኩ የተሰጠውን ተፈጥሮአዊ ኃይል ጠቃሚ በሆነ መንገድ ለማዋል በሕይወቱ ውስጥ እግዚአብሔርን ማኖር አለበት:: “ኃይሌን ወደ አንተ አስጠጋለሁ” በእኔ ውስጥ አንተ እንድትሠራ እፈቅዳለሁ ተብሏል:: እንግዲህ እግዚአብሔር በሕይወታችን የሚኖር ከሆነ ሁለንተናችን በኃይል የተመላ ማስተዋላችንም ጥበብ የበዛበት ይሆናል::

Monday, May 27, 2013

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ወደገላትያ ሰዎች ትንታኔው

የሐዋው የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት  ወደገላትያ ሰዎች ትንታኔ
የትንታኔው ዓላማ ፡ እግዚአብሔር  በዚህ መልዕክት ውስጥ ያስቀመጠልንን መለኮታዊ አሳቡን መረዳት ሲሆን ይህም ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን ስለሚገኘው ድኅነትና ጽድቅ እንዲሁም  የክርስትናን ሕይወት እንዴት መኖር እንደሚገባ ማሳየት ነው፡፡
መግቢያ
የመልዕክቱ ጸሐፊ
የገላትያ  መልዕክት ጸሐፊ ሐዋርያው ጳውሎስ መሆኑን ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንት ይስማማሉ፡፡
ሐዋርያው ጳውሎስ ማን ነው ?
በዚህ ስም ከመታወቁ በፊ ሳውል በመባል ይጠራ የነበረና  በአሕዛብ ምድር የሮም ግዛት በሆነችው በኪልቂያ ጠርሴስ ከቢንያም ነገድ የተወለደ አይሁዳዊ ነበር፡፡ ምንም እንኳ በዚያን ዘመን እንደዛሬው አሜሪካዊነት ሮማዊነት በቀላሉ የማይገኝ ቢሆንም  በሮም ግዛት መወለዱ ሮማዊ ዘግነት እንዲኖረው  አስችሎታል፡፡ ሐዋ 21፥39, 22፥22_29
ጳውሎስ በአሕዛብ ምድር ቢወለድም እድገቱ በአይሁድ ሕግና ሥርዓት መሠረት በታላቁ የብሉይ ኪዳን /የኦሪት ሕግ/ ምሁር እጅግ በተከበረው በገማልያል የኦሪትን መጻሕፍትና የአባቶቹን ወግ ጠንቅቆ እየተማረ ነበር፡፡ ሐዋ 22፥3, 5፥33_ 39 ለአባቶቹም ወግ ቀናተኛና በዘመኑ ከነበሩት የእምነት ክፍሎች ውስጥ ፈሪሳዊ ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ በክርስቶንስ  ያመኑትን ክርስቲያኖች የሚያሳድድና የሚያንገላታ  አደገኛ የቤተክርስቲያን ጠላት ነበር፡፡ እርሱም ስለራሱ ሲናገር “ በስምንተኛው ቀን የተገረዝሁ ከእስራኤል ትውልድ ከቢንያም ወገን ከዕብራውያን ዕብራዊ ነኝ ስለሕግ ብትጠይቁ ፈሪሳዊ ነበርሁ፡፡ ስለቅናት ብትጠይቁ ቤተክርስቲያንን አሳዳጅ ነበርሁ፡፡ በሕግ ስለሚገኝ ጽድቅ ብትጠይቁ ያለነቀፋ ነበርሁ” ይላል፡፡ ፊል 3፥5_7 ፣ ገላ 1፥13
ይሁን እንጂ በውስጡ የነበረውን ቅንነትና ታማኝነት ተገቢ ባልሆነ መንገድ ተሰማርቶ እየተጠቀመበት ስለነበረ በደማስቆ ጎዳና ላይ በብርሃን ነጸብራቅ ጥሪ ተላለፈለት፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ተመርጦ በራሱ በኢየሱስ ጥሪው ተላለፈለት፡፡ ጌታ ኢየሱስ በአገልግሎት ዘመኑ  የቀደሙትን ሐዋርያት ለሥራ የተሰማሩበት ቦታ ድረስ እየሄደ ከጠራቸው በኋላ”እኔ መረጥኋችሁ” እንዳላቸው ሁሉ፤ አሁንም ከትንሥኤውና ከዕርገቱ በኋላ ሳውልን ለአገልግሎት ጠራው፡፡ አስቀድሞ ከነበረው አፍራሽ  ዓላማው አንጻር ይህ ታላቅና የጌታ የምህረቱ መገለጫ የሆነው ጥሪ ደርሶት ምስጋና ሲያቀርብ “ለአገልግሎት ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለቆጠረኝ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ” ካለ በኋላ የራሱን ሕይወት ሲተርክ”አስቀድሞ ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላችም ምንም ብሆን ይህን አደረገልኝ ነገር ግን ሳላውቅ ባለማመን ስላደረግሁት ምሕረትን አገኘሁ” ብሏል፡፡1ጢሞ 1፥12_13፡፡


Friday, May 24, 2013

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት

ጸሎት
የማትመረመር ሁሉን የምትመረምር፤ የማትታይ ሁሉ በፊትህ የተገለጠና የተራቆተ፤ ሐሳባችንን የምታነብ በልባችን የሚመላለሰውን ምኞት የምትሰማ እግዚአብሔር ሆይ አባታችን ነህና ተመስገን:: ጌታችን ሆነህ የመገዛት ጸጋን ሰጥተኸናልና ተመስገን:: አምላካችን ሆነህ የአምልኮ መንፈስን ሰጥተኸናልና ተመስገን:: የጠፋውን ፈልገህ የምታመጣ ከበረትህም የምታስገባ የወደቀውን የምታነሣ የደከመውን በቃልህ ጉልበት የምታበረታና ለክብርህም የምታቆም አንተ ነህና ተመስገን::
የምንታመንለትን እውነት የምንጓዝበትን መንገድ የምንኖርበትን ሕይወት አንድ ልጅህን ጌታ ኢየሱስን ስለሰጠኸን ደግሞም አንተንና እርሱን በንጹሕ ዕምነት ማወቅንም የዘላለም ሕይወት ስላደረግህልን ተመስገን:: አንተን በማመን እንድንጸና በቃልህ በኩል መጽናናት እንዲሆንልን የፍቅርህ መልዕክት የሆነውን ቅዱስ መጽሐፍ ስለሰጠኸን ተመስገን::
ጌታ ሆይ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ያለውን እውነት በማስተዋል እንድንረዳ ዐይነ ልቡናችንን ታበራ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን:: አሜን!!

መቅድመ ነገር
           መጽሐፍ ቅዱስ ለምን ይጠናል?
የሰው ልጅ ባለአእምሮ ፍጥረት ነው:: ገና ጠባብና ምቹ ከሆነው ከእናቱ ማኅጸን ሰፊና አስቸጋሪ ወደሆነው ወደ ገሃዱ ዓለም ሲመጣ ማየት የሚችል ዐይን መስማት የሚችል ጆሮ መዳሰስ የሚችል እጅ እንዲሁም አጠቃላይ ሰውነት መቅመስና ጣዕምን መለየት የሚችልበት ምላስ ማሽተትና መዓዛን  መለየት የሚችልበት አፍንጫ ይዞ ነው የሚወለደው::
ይሁን እንጂ ከዚህ በላይ ለጠቀስኳቸውና በቁጥር ለመወሰን አስቸጋሪ ለሆኑት ስሜቶቹ ሁሉ ዋናውንና አስፈላጊውን እገዛ የሚሰጠው የሰውነቱ /የብልቶቹ ሁሉ/ ዋናው መሥሪያ ቤት (አዛዥ ባለስልጣን) አእምሮው ነው:: እንዲያውም በሰው ልጅ የአወላለድ ሂደት በመጀመሪያ የገሃዱን ዓለም የሚቀላቀለው ጭንቅላቱ /ራሱ/ ነው:: ጠንካራ በሆነውና ከአጥንት በተገነባው ደግሞ  የአጥንቱ ስፌት በሚያምረው የራስ ቅል ውስጥ ያለውን የሰው ልጅ ሁሉን ነገር የሚያውቅበትን የሚረዳበትን የሚገነዘብበትን ዋናውን የሰውነቱን ክፍል ይዞ ይወለዳል:: ዐይን፣ ጆሮና ሌሎችም የስሜት ሕዋሳት አጠቃላይ መረጃን በመሰብሰብ ለአእምሮ ያቀብላሉ:: አእምሮ ደግሞ የተቀበለውን መረጃ በየዐይነቱ በመለየት ያደራጃል፤ ያገናዝባል፤ ያብሰለስላል፤ ያንሰላስላል። በመቀጠልም አስፈላጊ የሆነውን ትርጉም በመስጠት ዕውቀት ያደርገዋል።
እንግዲህ ቁሳዊ በሆነው በዚህ ዓለም የሚኖረው የሰው ልጅ ሥጋዊ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ የሆኑትን እንዲሁም ተፈጥሮአዊ ጉዳዮችን ሁሉ ማጥናቱ የተለመደ ነው። ምክንያቱም ለማወቅ መፈለግና  ማወቅ ተፈጥሮአዊ ስጦታው ነውና። ስለሆነም ሰው ይልቁንም ክርስቲያን ሊያጠናቸው ከሚገቡት ነገሮች ውስጥ ቅድሚያ መስጠት ያለበት ለመጽሐፍ ቅዱስ ነው። ጥናት ከሚጠናው ነገር ጋር በቀጥታና በተዘዋዋሪ ግንኙነት ያላቸውን መረጃዎች በማሰባሰብና በማመሳከር ስለሚጠናው ነገር ጥልቅ ጭብጥ ወይም ጥቅል እውነት ላይ መድረስ ነው። ስለሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ከሚጠናበት ምክንያቶች ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው።

1.    እምነትን ለማጠንከር
እምነት የማናየውንና ተስፋ የምናደርገውን ነገር የሚያረጋግጥ ከሰው ልጅ የአማኝነት ተፈጥሮአዊ ዝንባሌ ውስጥ የሚፈልቅና የሚያድግ መንፈሳዊ ኃይል ነው። የሚያድግ ብቻም ሳይሆን የሚያሳድግም ነው፡፡“እንግዲህ ጌታን ክርስቶስ ኢየሱስን እንደተቀበላችሁት (እንዳመናችሁትበእርሱ ተመላለሱ ሥር ሰዳችሁም በእርሱ ታነጹ” በተባለውም መሠረት ክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ስለኃጢአታችንም ተላልፎ የተሰጠ ቤዛችን መሆኑን በማመን መንፈሳዊ ቤት ለመሆን የምንታነጽበት ነው። ቈላ 2፥6። እንዲሁም በዚህ በዘመን መጨረሻ ላይ የምንገኝ ክርስቲያኖች የእምነታችንን ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን የምናይበት የምንመለከትበትዐይናችንም ነው።  ዕብ 12፥2። ደግሞም ድኅነትን ያገኘንበትን ጸጋ የተቀበልንበት  ነው። ኤፌ 2፥8። ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌሉ የእረኛችንን ድምጽ ከጠላት ድምጽ ለይተን የምናውቅበት መሆኑን “በጎቹ ድምጹን ያውቃሉና ይከተሉታል” በማለት ይገልጻል። ድምጹን ማወቅ መስቀላችንን ተሸክመን እንድንከተለው ያስችለናል። ዮሐ 10፥4። የእረኛችን ድምጽ በቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ተጽፎ የተቀመጠልን መጽሐፍ ቅዱስ ስለሆነ ቃሉን ማወቅ እምነትን ማሳደግና እንዲያብብ ማድረግ ከዚያም የመንፈስ ፍሬ እንዲያፈራ ያስችላል፡፡
እንደየአማኙ ሁኔታ ታናሽ፣ ጎዶሎ፣ የሚያድግ፣ ታላቅ  እምነት ሊኖረን ይችላል። ታናሹም ወደ ታላቅነት፤ ጎዶሎውም በክርስቶስ ወደሚገኝ ሙላት ፤ የሚያድገውም የወይን ግንድ በሆነው በክርስቶስ ሆኖ  ፍሬ ማፍራት ታላቁም ከነውርና ከነቀፋ ርቆ ንጽሕናን ጠብቆ በቅድስና እየተመላለሰ እግዚአብሔርን በመምሰል መኖር የሚችለው ቃሉን በእምነት ሆኖ በማጥናት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ “የእግዚአብሔር ቃል በሙላት ይኑርባችሁ” ያለው እምነታችን በእውነትና በመንፈስ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያቆመን እንዲሆን  በቃሉ መጠንከር ስላለበት ነው፡፡ እንዲህ ከሆነ ደግሞ በውስጣችን ካለው ከእግዚአብሔር ቃል የተነሳ ፈቃዳችን ሁሉ ለእርሱ የተሰጠ ይሆናል፡፡ ቈላ 3፥16። “ዕለት ዕለት መጻሕፍትን እየመረመሩ ቃሉን በሙሉ ፈቃድ ተቀበሉ” ተብሎ የተነገረላቸው የቤርያ ሰዎች የቅዱስ ጳውሎስን ትምህርት ሰምተው ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር ለማመሳከር ወደ ምርምር የገቡት መጻሕፍትን ማጥናት በእምነታቸው ላይ የሚጨምረውን ጥንካሬና ዕድገት በማስተዋል ነው። ሐዋ 17፥11። በእግዚአብሔር ቃል እምነቱ የጠነከረለት አማኝ ደግሞ
·         ያመነውን ያውቃል   2ጢሞ 1፥12
·         በወንጌል አያፍርም   ሮሜ 1፥16
·         እግዚአብሔርን ብቻ ይሰማል   ሐዋ 4፥19
·         ወደ ግራም ወደ ቀኝም አይልም   ኢያ 1፥7
·         ስለ ኃጢአቱ ያለቅሳል   ማቴ 26፥75  እነዚህና የመሳሰሉት ጥቅሞች ስለሚኖሩት መጻሕፍትን በማጥናት እምነትን ማጠንከር አግባብ ነው።

2.   ለመታዘዝ
መጽሐፍ ቅዱስን ስናጠና ለቃሉ በመታዘዝና ባለመታዘዝ የሚኖረውን የአቋምና የሕይወት ልዩነት እንረዳለን። ለቃሉ መታዘዝ የጽድቅ ባርያ /አገልጋይ/ ሲያደርግ አለመታዘዝ ደግሞ  የኃጢአት ባርያ ያደርጋል። ስለዚህ ቃሉን ማጥናት ለተረዱት እውነት ለመታዘዝ መሆን አለበት።  ይህን መድረሻ ግቡ አድርጎ የሚያጠና ሰው የጥናቱ መሠረት እምነት ስለሚሆን ላወቀው እውነት መታዘዝ አይከብደውም። የእግዚአብሔር ቃል ባጠናነው ቁጥር እምነታችንን እንደሚያጠናክር ሁሉ አመለካከታችንን ያስተካክላል፤ ግንዛቤያችንን ያሰፋል፤ ጠንካራውንም ልባችንን ይሰብራል።  እንድንኖረውም ያስችለናል። መታዘዝ በተረዱት እውነት መኖር ማለት ነውና። በጌታ ዘመንም ይሁን በሐዋርያት ዘመን ለወንጌሉ አገልግሎት እንቅፋት ሆነው የነበሩት የአይሁድ ካህናት የእግዚአብሔር ቃል እየሰፋ ሲሄድ እነርሱም እውነቱን ሲረዱ ብዙዎቹ ለእግዚአብሔር ቃል ታዝዘዋል። ሐዋ 6፥7። ጌታም በወንጌሉ ምሳሌ መስሎ ሲያስተምር ለቃሉ የሚታዘዘውን ልባም ሰው ሲለው ለቃሉ የማይታዘዘውን ደግሞ ሰነፍ ሰው በማለት ገልጾታል። ማቴ 7፥24። ቅዱስ ያዕቆብም ለተበተኑት ክርስቲያኖች በጻፈው መልዕክቱ ”ቃሉን የምታደርጉ ሁኑ“ ብሏል ያዕ 1፥22።
መታዘዝ በሥጋዊም ሕይወት ይሁን በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ያለው ጠቀሜታ በቃል ተዘርዝሮ  በጽሑፍ ተተንትኖ የሚያልቅ አይደለም። አንድ የሥነ ሕንጻ ባለሙያ ለተማረውና ላጠናው ትምህርት ታዛዥ ሲሆን እጅግ በጣም ጥሩ ሙያተኛ ይሆናል። በጊዜ ሂደትም ትምህርቱን በተግባር ሲያዳብረው ደግሞ  በጣም ተፈላጊና በሥራው ስኬታማ ይሆናል። አንድ መጽሐፍ ቅዱስ አጥኚ የሚያጠናው ለተረዳው እውነት ለመታዘዝ  ከሆነም በቃሉ አማካኝነት ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረው ኅብረት እየጠነከረ ዘወትር የእግዚአብሔር ፈቃድና  እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውን ነገር በመሥራት ይተጋል። መታዘዝ በድርጊት ይገለጣልና።