Friday, June 28, 2013

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ወደ ገላትያ ሰዎች ትንታኔ


ክፍል ሦስት

“ራሱን ሰጠ”
“ክፉ ከሆነ ከአሁኑ ዓለም ያድነን ዘንድ እንደ አምላካችንና እንደ አባታችን ፈቃድ ስለ ኃጢአታችን ራሱን ሰጠ” ገላ 1፥4

አሁን የሚለው የጊዜ ቀመር ስያሜ ቀጣይ የሆነ የሕይወት ዑደት ማኅተም ነው:: እኔ አሁን የሚለውን ቃል ለመጻፍ ስጀምር አሁን ነበር:: ስላለፍኩት ደግሞ ቅድም ሆኗል:: የአሁኑ አሁን ቅድም የሚለውን ቃል ለመጻፍ ነው ያገለገለኝ:: መጽሐፍ ቅዱስ መለኮታዊ እስትንፋስ እንደመሆኑ አጠቃላይ መልዕክቱ ከጊዜ አንጻር ሲተመን አሁን በተባለው ጊዜ ላይ ልዩ  ትኩረት አለው:: ዛሬ ሃያ አራት ሰዓታትን ሲይዝ አሁን ግን ያለንበትን ቅጽበት ብቻ የሚወክል ነው:: ባለፈውና በሚመጣው ቅጽበት መካከል ያለች ሰዓት የማንነታችን ልዩ መገለጫ ናት::
 
በሕይወት ውጣ ውረድ ውስጥ የሚፈራረቁ አዎንታዊና አሉታዊ ነገሮች ሁሉ እየተከሰቱ የሚያልፉት  ቅድም፣አሁንና ኋላ  በተባሉት የጊዜ ሰንሰለታማ ሂደት ውስጥ ነው ፡፡ሐዋርያው ቅድም የነበርንበት፣ አሁን ያለንበትና ጌታ ቢፈቅድ በኋላ የምንኖርበት ይህ ዓለም ክፉ እንደሆነ ይገልጻል:: የአሁኑ ዓለም መልካምና ክፉ ነገር ሊከናወንበት ይችላል:: አዲሱ ሰው ክርስቶስን ለብሰው እርሱ ውበት መልክ የሆናቸው ሁሉ መልካሙን ያደርጋሉ:: አንድ ጊዜ በክርስቶስ ስለጸደቁ ራሳቸውን የክፉ ነገር ባርያ አያደርጉም የክርስቶ ልብ አላቸው :: ከክርስቶስ ውጭ ያሉት ደግሞ ክፉን ያደርጋሉ:: የክፉ ድርጊት መነሻው በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ አለማመን ነው:: የአሁኑ ዓለም ተብሎ የተገለጸው የዕለትተዕለት የሰው ኑሮ  /ሕይወት/ ነው:: የዓለም ክፋ  የሚገለጠው በሰው ኑሮ ውስጥ ነውና::


ዓለም ክፉ የተባለበት ምክንያት ገዥውም ክፉ ስለሆነው ነው:: እርሱ ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ በሰው ማንነት ውስጥ የገውን የክፋት አስተሳሰብና አመለካከት እንዲሁም የክፋት ስሜት እየተጠቀመ የዓለምን ሥርዓት በነውር ሥራዎች እየመላ ብዙዎችን ለዘላለም ጥፋት ያሚመራ ነው፡፡ “ዓለምም በሞላው በክፉ እንደተያዘ እናውቃለን” 1ዮሐ 5፥19:: እንዲሁም “የዚህዓለም አምላክ የማያምኑትን ሐሳብ አሳወረ” ተብሏል:: 2ቆሮ 4፥4:: የዚህ ዓለም አምላክ የተባለው ዲያብሎስ ነው:: እርሱ ደግሞ ሰው የልቡናው ዐይን እንዳይበራና የተደረገለትን መዳን እንዳይረዳ ይፈትናል፤ ያደርጋልም:: ከክርስቶስ መንግሥት ውጭ ያሉ በዲያብሎስ ግዛት ውስጥ የሚኖሩ ብዙዎች በራሳቸው ክበብ ውስጥ የሐሰት ሰላምና  ፍቅር አላቸው:: ጌታም ይህን ለማስረዳት እኔ የምሰጣችሁ ሰላም ዓለም እንደሚሰጣችሁ አይደለም ብሏል:: እንዲሁም “ዓለም የራሱ የሆነውን ይወዳል” ብሏል:: የተረጋጋ የሚመስል ኑሮና መተሳሰብ ያለበት የሚመስል ፍቅር በብዙ ዓለማውያን ዘንድ ሊታይ ይችላል:: ግን ሁሉም ሐሰት ነው::
 
እንግዲህ ሐዋርያው ይህን እውነት ለማስረዳት የአሁኑን ዓለም ኑሮ/ ሕይወት/ ክፉ መሆኑን አስገንዝቧል:: ደግሞም የአሁኑ ዓለም አለ እንጂ ዓለም አላለም:: ምክንያቱም ክርስቲያኖች ተስፋ የምናደርገውና ክፉው የማይሰለጥንበት እውነተኛው ጌታ ብቻ የሚመራውና የሚያስተዳድረው ዓለም ስላለ  ከመጪው ዓለም ለመለየት የአሁኑ ዓለም ብሏል::
 
በርግጥ የአሁኑ ዓለም ምንም እንኳ በክፉ ቢያዝም በክርስቶስ ላሉት ግን የሥራ ቦታ ነው:: ስለዚህም ነው ሐዋርያው “በሥጋ መኖሬ ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን ምን እንድመርጥ አላስታውቅም:: በእነዚህ በሁለቱ እጨነቃለሁ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፤ ከሁሉም ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና:: ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው:: ያለው:: ፊል 1፥22::

Friday, June 7, 2013

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ወደ ገላትያ ሰዎች ትንታኔ

                                         ጸሎት
ሕያው ስም ያለህ፣ሕልውናህን ጊዜ የማይወስነው አንተ እግዚአብሔር ነህና ተመስገን፡፡ ፍጹምነትህ አርዓያችን ነው፡፡ርኅራኄኅ መጽናኛችን ነው፡፡ ምሕረትህ መኖሪያችን ነውና ተመስገን፡፡ በልባችን ውስጥ የሚመላለስው የሰውነት ድካማችን ወደ ክፉው እንዳይወስደን ራሳችንን መግዛት የምንችልበትን ጸጋ አብዛልን፡፡  በሥላሴነትህ ውስጥ ያለውን አንድነትህን እንድንረዳ፣አንድነትህ ውስጥ ያለውን ሦስትነትህን እንድንገነዘብ ዓይነ ልቡናችንን አብራ፡፡በቃልህ ራሳችንን ከማየትና ከመመርመር ይልቅ ሌሎችን እንዳንከስበት ማስተዋልን አብዛልን፡፡ መጻሕፍትን የመመርመርን ጥበብና ያገኘነውን እውነት እንድንጠቀምበት አትጋን፡፡ አሜን
                 ክፍል ፪
ከሙታን  ባስነሣው
ጳውሎስ  ለፊልጵስዩስ  ቤተክርስቲያን በጻፈው መልዕክቱ  “እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን  መቀማት እንደሚገባ  ነገር አልቆጠረውም” በማለት አብና መንፈስ ቅዱስ ያልሆኑትን እርሱ በተለየአካሉ ሰው ሲሆን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያለውን አንዲት ሥልጣን የሚወስድበት ማንም እንደ ሌለና እንደማይኖር አስገንዝቧል፡፡ፊል 2፥6፡፡ እውነት ነው እርሱ ራሱን ባዶ ቢያደርግም ፣የባሪያውን መልክ ቢይዝም፣ራሱን ቢያዋርድና ለመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ቢሆንም  ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ እግዚአብሔር ነው፡፡
ነገር ግን ጳውሎስ አንዱን አንሺ ሌላውን ተነሺ  አንዱን  ከሙታን መካከል ቀስቃሽ ሌላውን ተቃስቃሽ እያደረገ የጻፈው ለምንድነው ?::የተፈለገው ቁም ነገር ክርስቶስ ሞቶ ከተቀበረ በኋላ ከሙታን መካከል ተለይቶ መነሣቱን ማወጅ ብቻ አይደለም፡፡የክርስቶስ ትንሣኤ ቀድሞ በተዓምራት ይነሱ እንደነበሩት ሰዎች ተመልሶ ለመሞት አይደለምና፡፡ ነገር ግን የኃጢአትን ኃይል ለመግደልና የሞትን ስልጣን ለመሻር ነው፡፡በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ውስጥ ያለውን ይህንን ታላቅ ኃይል በአይሁድ ዕምነት ልባቸው ለታወረ ሰዎች ለማስገንዘብና በክርስቶስ እንዲያምኑ ለማድረግ ነበር፡፡
  “እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ  ምሳሌ ሆኖ . . .” እያለ ኢየሱስ ክርስቶስ ምንም ልጅ ቢሆን ከአባቱ ጋር የባሕርይ አንድነት እንዳለው ያስረዳል:: ዕብ 1፥3:: ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌሉ “በመጀመሪያው ቃል ነበረ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ” ብሏል:: ዮሐ 1፥1:: ኢየሱስ ክርስቶስም ራሱ “እኔና አብ አንድ ነን” በማለት በእርሱና በባሕርይ አባቱ በአብ መካከል ያለውን አንድነት ገልጿል:: ዮሐ 10፥30:: ሐዋርያው ኢየሱስ ክርስቶስን ከሙታን ያስነሣው እግዚአብሔር አብ እንደሆነ መግለጹ ታዲያ በአብና በወልድ መካከል ያለውን መለኮታዊ አንድነት ለመጣስ አይደለም፡፡መልዕክቱ የተጻፈው ስለክርስቶስ የማይገባ ግንዛቤ ለነበራቸው ቢሆን ኖሮ ከላይ የዘረዘርኳቸው ሥነመለኮታዊ እሳቤዎች ሁሉ በተጻፉ ነበር:: የስህተቱን ትምህርት ያመጡት ሕገ ኦሪትን ብንተው ቅጣት ይመጣብናል ብለው የሚፈሩ ሰዎች እንጂ ስለ ክርስቶስ ምንም ግንዛቤ ያልነበራቸው አይደሉም:: ስለዚህም ሐዋርያው የሕግ አስፈላጊነት ሙሉ ለሙሉ መቅረቱን ግልጽ አድርጎ ለማስገንዘብና በዚህ ፈንታ በክርስቶስ መስቀልና ትንሣኤ ሁሉም ነገር ተሟልቶ መስጠቱን አጥርቶ ለማስረዳት ነው ::
ዓላማው የክርስቶስን መለኮትነት ማስረዳት ቢሆን ኖሮ እርሱም እንደ ወንገሌላዊው ዮሐንስ በመጀመሪያ ቃል ነበረ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ እያለ የቃልን /የክርስቶስን/ እግዚአብሔርነት ብቻ አጉልቶና በሦስቱ አካላት መካከል ምንም ልዩነት እንደሌለ አሳይቶ ሐሳቡን መጠቅለል ይችል ነበር:: የክርስቶስን መለኮታዊነት ብቻ አጉልቶ መናገር በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ የሚጨምረው ነገር የለም:: ስለእግዚአብሔር እግዚአብሔርነት ጥንትም ሲነገር ነበርና:: ነገር ግን “ከሙታን ባስነሣው” የሚለው ሐረግ የሰው ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ያገኘውን ትልቅ ጥቅም የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ሆኖም ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ ለመነሣት ኃይል የሌለው መሆኑን አይደለም የሚናገረው፡፡ መቼም በኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑ ምድራዊና ሟች የሆነ ሰውነት የተሸከሙ ሰዎች በጥላቸው ሙታን እያስነሱ፤ በጨርቃቸው ድውይ እየፈወሱ ኢየሱስ ሞትን ድል ማድረግ አቃተው ብሎ ማሰብ እብደት ወይም ጅልነት ነው:: ሐዋ 5፥15፣ 19፥11-14:: ኢየሱስም ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስት ቀን አስነሣዋለሁ” እያለ ስለ ሞቱና ትንሣኤው ይናገር ነበር::         ዮሐ 2፥19:: እንዲሁም “ነፍሴን ደግሞ አነሳት ዘንድ አኖራለሁና  .  እኔ በፈቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወሰዳትም” ብሏል:: ዮሐ 10፥18:: ስለዚህም ከሙታን ባስነሳው በእግዚአብሔር አብ በማለት እግዚአብሔር አብ ኢየሱስ ክርስቶስን ከሙታን እንዳስነሳው ሲገልጽ፤ ወልድ /ኢየሱስ ክርስቶስ/ ደግሞ መስራት የነበረበትም ነገር አብን ማክበር መሆኑን  ማስረዳት ነው:: ኢየሱስ “እኔ ላደረገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርሁህ” ብሏል ዮሐ 17፥4::
እንግዲህ ትውልድን በፍርሃት እያስጨነቀ በኃጢአት ምክንያት ሰልጥኖ የነበረው ሞት በክርስቶስ ላይ ለምን ኃይል አጣ? ክርስቶስ በሞት ሥልጣን ቁጥጥር ሥር ውሎ ወደ መቃብር ሲወርድ በአምላክነት ሥልጣኑ ከሞት ባለሥልጣን ጋር በመቃብር ውስጥ ለመታገል ቀጠሮ ይዞ ነበርን? አይደለም:: የክርስቶስ መሞት ዓላማው በአምላክነት ሥልጣኑ ታግሎ ማሸነፍ ቢሆን ኖሮ ቀድሞውኑ መሞት አያስፈልገውም ነበር:: አምላክ ነውና:: ያም ብቻ አይደለም ሥጋን መዋሃድና ሰው መሆን አያስፈልገውም ነበር:: በእግዚአብሔርነቱ ሥልጣን ሥጋን ሳይዋሃድ ሞትን መቅጣት ይችል ነበርና:: ግን አላደረገውም:: በሥልጣኑ ቀላያትን ነድሎ ምድርን በንፍር ውሃ ያጠፋ፣ ሕዝቡን ባሕር ከፍሎ ያሻገረ፣ ጠላትን በባሕር ውስጥ ያሰጠመ፣ በበረሃ መና የሰጠ ሌሊቱን በብርሃን ቀኑን በደመና ሕዝቡን ይመራ የነበረ ከዓለት ላይ ውሃ ያፈልቅ የነበረና ሌሎችንም ዘርዝረን የማንፈጽማቸውን ሥራዎች በመለኮታዊ ሥልጣኑ የሠራ ሞትንም መቅጣት ይችል ነበር::

Sunday, June 2, 2013

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ወደ ገላትያ ሰዎች ትንታኔ

                                        ምዕራፍ 11-3
                                          
በኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታንም ባስነሳው በእግዚአብሔር አብ ሐዋርያ የሆነ እንጂ ከሰዎች ወይም በሰው ያልሆነ ጳውሎስ ከእኔም ጋር ያሉት ወንድሞች ሁሉ ወደ ገላትያ አብያተክርስቲያናት

                                              ክፍል
ከቅዱስ ጳውሎስ መልዕክታት ውስጥ በኃይል የተጀመረና እስከ ፍጻሜውም ድረስ ጠንካራ የአዲስ ኪዳን ትምህርተ መለኮት ያለበት መልዕክት ወደ ገላትያ የላከው  መልዕክት ነው:: ኃይለኛነት የጠላት ወይም የምንደኛ እረኛ ጠባይ ቢሆንም ሁልጊዜ በጨዋነትና በተረጋጋ ሁኔታ ደቀ መዛሙርትን ማስተማር ግን አግባብ አይደለም:: ተግሳጽን የያዘ ሊያርም የሚችል የኃይል ንግግር የሚያስፈልጋቸው ጊዜ አለና:: ጌታ ኢየሱስ ደግና አዛኝ ሆኖ ሳለ ደቀ መዛሙርቱን አንዳንድ ጊዜ በበረከት ቃል ሲናገራቸው ሌላ ጊዜ ደግሞ በኃይለ ቃል ይናገራቸው ነበረ:: ጌታችን ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ፊልጶስ ቂሣርያ በደረሱ ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ አንድ ጥያቄ አቅርቦላቸው ነበር:: የእጁን ታምራት ሲያዩ  የቃሉን ትምህርት ሲሰሙ አብረውት ከመዋልና ከማደራቸው  አንጻር  መረዳታቸውን እንዲረዱ መጠየቅ ነበረባቸው:: ጌታ ኢየሱስምሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል?” አለና ሌሎች ሰዎች ስለእርሱ ያላቸውን ግንዛቤ ከደቀመዛሙርቱ ለመስማት  ጠየቀ:: እነርሱም የሰሙትን አሰሙት::
ጥያቄው ቀጠለእናንተስ እኔን ማን እንደሆንሁ ትላላችሁ?” አላቸው:: ዝምታ ሰፈነ:: ሁሉም ምላሽ ለማግኘት ወደ ልቡናው ጓዳ ገባ:: እያንዳንዱም በሐሳቡ በራሱ ልብ ውስጥ ይሯሯጥ ጀመር:: እነርሱ ጥያቄውን ከአፉ ሳይጨርስ መልሱን መስጠት ነበረባቸው:: ነገር ግን ስለ ኢየሱስ ለመናገር መረጃ ከሰማይ ካልተለቀቀ በስተቀር ብልጭታን ያህል መረዳት ማገኘት ከባድ ነው:: ስለዚህም ደቀ መዛሙርቱ እርስ በእርስ ለመተያየት ወይም ወደ ኢየሱስ የመመልከቻም ጊዜ አልነበራቸውም:: ሁሉም ውስጣቸው ገብተው ተደበቁ::
ይገርማል! ጌታ ግን አሳብን የሚያነብ በልብ ውስጥ የሚመላለሰውን ምኞት የሚያደምጥ እንደመሆኑ ፈጣን ምላሽ ባለመስጠታቸው ሊነቅፋቸው አልወደደም:: ጠበቃቸው:: ዝምታው በሰፈነበት ሰዓት ጴጥሮስ ለካ በአካል እንጂ በመንፈስ መካከላቸው አልነበረም:: ስለ እርሱ በብቃት የሚገልጽለትን መንፈስ ቅዱስን ለማስተናገድ ልቡናውን እያዘጋጀ ነበር:: ከጥቂት ቆይታዎች በኋላአንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህየሚል ድምጽ  ከጴጥሮስ ወጣ:: አይደለም ሌሎቹ ደቀ መዛሙርት ራሱ ጴጥሮስም ሳይደነግጥ አልቀረም::
 አስቀድሞስ ጌታየምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁምብሏቸው አልነበር ?   ማቴ 1019:: ሁሉም ግን ይህን አላሰቡም ነበር:: ጴጥሮስ ግን ተሣካለት:: ጌታም አስቀድሞ በዮርዳኖስ ስለልጁ የመሰከረ አብ አሁንም  በጴጥሮስ ሆኖ እየተናገረ መሆኑን ስላወቀየዮና ልጅ ስምዖን ሆይ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህአክሎምበዚህችም ዓለት ላይ ቤተክርስቲያኔን እሠራለሁአለው:: ዓለት ያላትአንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህየምትለውን እምነት ነው፡፡  ማቴ 1616-18::
ጌታ ኢየሱስ በአንድ ሥፍራብፁዕብሎ የባረከውን ጴጥሮስን ወዲያውኑ እርሱ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚወጣና በዚያም ብዙ መከራ ደርሶበት እንደሚሞት በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ ለደቀመዛሙርቱ ሲገልጥላቸው ጴጥሮስአይሁንብህ ጌታ ሆይ ይህ ከቶ አይደርስብህም ብሎ ሊገስጸው ጀመርጌታምወደ ኋላ ሂድ አንተ ሰይጣን የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና እንቅፋት ሆነህብኛልብሎታል  ማቴ 1622-23:: አንድ እረኛ /መምህር/ መልካም የሚባለው ተገቢውን ነገር በተገቢው ጊዜና ቦታ መናገር ሲችል ነው:: ጌታ ደግሞ ቸር እረኛ ፣ደግ እረኛ ነው:: ነገ ኃላፊነት የሚቀበሉት ደቀ መዛሙርቱ በሰውኛ ስሜትና አመለካከት ተይዘው የእግዚአብሔርን ሐሳብ ሳያገለግሉ እንዳይቀሩ ይፈልጋል:: ስለዚህ ጴጥሮስን የሰይጣን አሳብ አስተናጋጅ ሆኖ ሲያገኘው ገሰጸው:: በሌላ ጊዜ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ጌታ ባቀረበው ምሳሌ ግራ ተጋብተው ስለነበረ ጴጥሮስ ወደ ጌታ ጠጋ ብሎጌታ ሆይ ምሳሌውን ተርጉምልንሲለው ጌታ ኢየሱስም መልሶእናንተ ደግሞ እስከ አሁን የማታስተውሉ ናችሁን?” አላቸው:: ማቴ 1516:: እነዚህ የግሳጼ ንግግሮች ማስጠንቀቂያ ሆኗቸው ጌታችን በያዕቆብ ጉድጓድ አጠገብ ከሰማርያዊቱ ሴት ጋር ሲነጋገር አይተው አንዳች ለመናገር አልደፈሩም ነበር:: ዮሐ 427::